Agrégateur de contenus

null የማኅበራዊ ትሥሥር ገፆች የተሳሳቱ መረጃዎችን የሚያጋልጥ ሥርአት ተግባራዊ እንዲያደርጉ ተጠየቀ

የማኅበራዊ ትሥሥር ገፆች የተሳሳቱ መረጃዎችን የሚያጋልጥ ሥርአት ተግባራዊ እንዲያደርጉ የአውሮፓ ኅብረት ጠየቀ፡፡

የአውሮፓ ህብረት ስራ አስፈፃሚ አካል ጎግል፣ ፌስቡክ፣ ዩቲዩብ እና ቲክ ቶክን ጨምሮ ሌሎች የማህበራዊ ትስስር ገጾች በሰው-ሰራሽ አስተውሎት (Artificial Intelligence) አማካኝነት ጥበብ በተሞላበት መንገድ የተፈጠሩ ፎቶዎችን፣ ቪዲዮዎችን እና ጽሑፎችን እንዲለዩ እና ተጠቃሚዎችን እንዳያሳስቱ በግልፅ እንዲያሳውቁ (Labeling) ጠይቋል።

የአውሮፓ ኅብረት ኮሚሽን ምክትል ፕሬዚዳንት ቬራ ጆውሮቫ በሰጡት ማሳሰቢያ በተለይ አሁን አሁን በሰው-ሰራሽ አስተውሎት አማካኝነት አሳሳች ይዘቶች፣ ምስሎችን እንዲሁም ድምጽን ጭምር በሠከንዶች ውስጥ አስመስለው መፍጠር የተቻለበት ጊዜ ላይ በመደረሱ የሐሰት መረጃዎችን መዋጋት አዲስ ፈተና ሆኖ ብቅ ማለቱን ተናግረዋል፡፡

እንደ ጎግል፣ ማይክሮሶፍት እና ሜታ ያሉት ፕላትፎርም ባለቤቶች የሀሰት መረጃ ስርጭትን ለመከላከል በአውሮፓ ህብረት የቀረበውን ህግ የፈረሙ በመሆናቸው በመጪው ሐምሌ ወር ላይ ይህንን መከላከል የሚያስችል አሰራር በመተግበሪያዎቻቸው ላይ መጠቀማቸውን ሪፖርት ማድረግ ይኖርባቸዋል ሲሉ ም/ፕሬዝዳንቱ ተናግረዋል።

በሀገራችን ኢትዮጵያም ከዲጂታል ቴክኖሎጂ መስፋፋት እና የመረጃዎች ስርጭት ከመበራከቱ ጋር ተያይዞ ሀሰተኛ እና አሳሳች መረጃዎች በማህበራዊ ትስሰር ገጾች ላይ በብዛት ተደራሽ ይደረጋሉ፡፡

ይህንኑ ተግባር ለመከላከል የኮምፒዩተር ወንጀልን ለመደንገግ በወጣ አዋጅ ቁጥር 958/2008 ንኡስ ክፍል ሁለት አንቀጽ 9 እና 10 ማንኛውም ሰው የሌላውን ሰው መብት ወይም ጥቅም ለመጉዳት ወይም ለራሱ ወይም ለሌላ ሰው ተገቢ ያልሆነ ማናቸውንም መብት ወይም ጥቅም ለማግኘት ወይም ለማስገኘት በማሰብ አሳሳች የኮምፒዩተር ዳታዎችን ማሰራጨት፣ ከሦስት እስከ አስር ዓመት ጽኑ እስራት እና ከብር 10,000 እስከ ብር 100,000 በሚደርስ መቀጮ እንደሚቀጣ ይደነግጋል፡፡

በመሆኑም ሁሉም ሰው በሳይበር ምህዳሩ ላይ መረጃን ሲቀበል እና ሲያሰራጭ ጥንቃቄ ማድረግና ትክክለኛነቱን (ተአማሚነቱን) ማረጋገጥ ይገባዋል፡፡