127ኛው የዓድዋ ድል በዓል በደማቅ ሁኔታ ተከበረ

[#if smallImage??]
    [#if smallImage?is_hash]
        [#if smallImage.alt??]
            ${smallImage.alt}
        [/#if]
    [/#if]
[/#if]

የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አአስተዳደር (ኢመደአ)፣ የሰላም ሚኒስቴር፣ የአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢስቲትዩት እና የፋይናንስ ደህንነት አገልግሎት አመራሮች እና አባላት 127ኛውን የዓድዋ ድል በዓል በደማቅ ሁኔታ አከበሩ፡፡

በበአሉ ላይ የተገኙት የጥንታዊት ኢትዮጵያ ጀግኖች አርበኞች ማህበር ተወካይ  አቶ ጥላሁን ጣሰው የእንኳን አደረሳችሁ መልክት ባስተላለፉበት ወቅት እንዳሉት አባት እና እናት አርበኞች ከምእራባውያን ወረራ በጽናት ታግለው አገራችንን እንዳቆዩ ሁሉ የአሁኑም ትውልድ ከማንኛውም ጥቃት እና ተጽእኖ ሀገሩን መጠበቅ እንዳለበት አሳስበዋል፡፡

የኢመደአ ዋና ዳይሬክተር የተከበሩ አቶ ሰለሞን ሶካ በበኩላቸው የዓድዋ ድል በዓል በመላው ዓለም የሚገኙ ኢትዮጵያውያን ኩራት ብቻ ሳይሆ ሁሉም ጥቁር ህዝቦች አንገታቸውን ቀና አድርገው የሄዱበት ታላቅ በዓል እንደሆነ ገልጸዋል፡፡ ይህ ግን ታሪክ እንደሆነ እና ለአሁኑ የሀገር እድገት እና ሉዓላዊነት መሰረት እንጂ ዋስትና እንደማሆን አስረድተው፤ ትውልዱ የቴክኖሎጂ እና የእውቀት ባለቤት በመሆን ከምእራባውያን ጥገኝነት ነጻ በመውጣት ደማቅ ታሪክ ሰርቶ ድሉን ማስቀጠል እንደሚኖርበት አስገንዝበል፡፡ ዋና ዳይሬክተሩ አያይዘው እንደገለጹት ዘመኑ የሚጠይቀው አርበኝነት እውቀትን በመታጠቅ ድህነትን እና ኋላ ቀርነትን ድል ማድረግ ነው ብለዋል፤ ይህ ግን እንዲሁ በነጻ የሚገኝ ሳይሆን መስዋእትነትን በመክፈል ጭምር እንደሆነ አስገንዝበዋል፡፡ የአድዋ ድል ጀግኖች ውድ ሕይወታቸውን ገብረው ነጻ ሃገር እንዳስረከቡን ሁሉ የዛሬው ትውልድም ድህነትን በእውቀትና በጥበብ ጦር ድል በማድረግ የበለጸገች ኢትዮጵያን ለመጪው ትውልድ ማስረከብ ይኖርበታል ብለዋል፡፡ በመጨረሻም  ኢመደአ የሃገራችንን የሳይበር ደህንነት በመጠበቅ የዲጂታል ሉዓላዊነታችንን ለማረጋገጥ ልክ እንደ አድዋ አርበኞች ሁሉ በጀግንነት እና በጽናት እንደሚሰራም ዋና ዳይሬክተሩ በአጽንኦት ተናግረዋል፡፡

የሰላም ሚንስቴር ሚኒስትር ድኤታ አቶ ታ ደንደአ በበኩላቸው ዛሬም ወረራ መልኩን ቀይሮ በቴክኖሎጂ እና በባህል እንዳለ ገልጸዋል፡፡ ገንዘብ ከፍለን በምንጠቀምበት ማህበራዊ ሚዲያ የሀገርን ሉላዊነት የሚያፈርስ ተልእኮ እየገዛን እርስ በእርሳችን በመገዳደል የአገርን ሉዓላዊነት አደጋ ላይ ከሚጥል ተግባር መቆጠብ እና የአቶቻችንን አንድነት፣ ጀግንነት እና ጽናት ወስደን የተሻለ አገር መገንባት እንደሚገባን አሳስበዋል፡፡

የፋይናንስ ደህንነት አገልግሎት ዋና ዳይሬክተር አቶ ሙሉቀን አማረ ባስተላለፉት መልዕክት የአድዋ ድል ጀግኖች አንድነትን ሃይል በማድረግ በጀግንነት እና በጽናት ታግለው ጠላትን ድል እንዳደረጉ ሁሉ የዛሬው ትውልድም አንድነቱን፣ ጀግንነቱን እና ጽናቱን ድህነትን ድል ለማድረግ በሚደረገው ትግል ላይ በማዋል የበለጸግች ሃገርን ለተተኪው ትውልድ ማስተላለፍ እንደሚገባው ገልጸዋል፡፡  

የአርፊሻል ኢንተለጀንስ  ም/ዋና ዳይሬክተር ዶ/ር ታዬ ግርማ በአሉን አስመልክተው ባደረጉት ንግግር ጥንት አባቶቻችን ጥቁር ሕዝብ በነጭ መገዛት አለበት የሚለውን አስተሳሰብ  በጽኑ ተጋድሏቸው ቀይራዋል፡፡ እኛም ዛሬ የቴክኖሎጂ ባለቤት በመሆን እና ለመልካም ነገር በማዋል የሀገራችንን ሰላም እና ደህንነት አስጠብቀን ለሚቀጥለው ትውልድ ሌላ ድል ማስረከብ አለብን ብለዋል፡፡

በመጨረሻም የጥንታዊት ኢትዮጵያ ጀግኖች አርበኞች ማህበር አባል እና ተወካ አቶ ጥላሁን ጣሰው የሀገርን አንድነት የመጠበቅ አደራን እና ሰንደቅ አላማውን ከአራቱም ተቋማት ለተወከሉ ወጣቶች አስረክበዋል፡፡