የሰሜን ዕዝ ላይ የደረሰው ጥቃት 2ኛ አመት መታሰቢያ ተካሄደ

[#if smallImage??]
    [#if smallImage?is_hash]
        [#if smallImage.alt??]
            ${smallImage.alt}
        [/#if]
    [/#if]
[/#if]

የሰላም ሚኒስቴር፣ የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር፣ የኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት፣ እና የፋይናንስ ደህንነት አገልግሎት በጋራ በመሆን ጥቅምት 24 በመከላከያ ሰራዊት የሰሜን ዕዝ ላይ የደረሰው ጥቃት ሁለተኛ አመት መታሰቢያ በተለያዩ መርሃ ግብሮች አካሄደዋል፡፡

ጥቅምት 24/2013 ዓ/ም በአሸባሪው የህወሃት ቡድን በሀገር መከላከያ ሰራዊት ሰሜን እዝ አባላት ላይ የደረሰው ጥቃት እና ሃገራዊ ክህደት ሁለተኛ አመት መታሰቢያ “ስለ ኢትዮጵያ የከፈላችሁትን አንረሳም” በሚል መሪ መልዕክት የአራቱ ተቋማት ከፍተኛ አመራሮችና ሰራተኞች በተገኙበት ታስቦ ውሏል፡፡

በመታሰቢያ መርሃ-ግብሩ ላይ ተገኝተው መልዕክት ያስተላለፉት የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር ዋና ዳይሬክተር የተከበሩ አቶ ሰለሞን ሶካ በመከላከያ ሰራዊታችን ሰሜን እዝ ላይ ከደረሰው ክህደት አንስቶ እስካሁን በመከላከያ ሰራዊት እና የጥምር ፀጥታ ኃይሉ እየተከፈለ ያለው መስዋዕትነት ታሪክ ሁሌም ሲዘክረ ይኖራል ብለዋል፡፡ ይህ መስዋዕትነታቸውም መና ሆኖ እንዳልቀረና የኢትዮጵያ አሸናፊነት እንደተረጋገጠ ገልጸዋል፡፡

አያይዘውም ዋና ዳይሬክተሩ እንዳሉት በዚህ ጦርነት ማንም ኢ-ህገመንግስታዊ ኃይል ኢትዮጵያን ወግቶ ማሸነፍ እንደማይችል እና የውጪ ታሪካዊ ጠላቶቻችንም የኢትዮጵያን አንድነት መናድ እንደማይችሉ ማሳያ ነው ብለዋል፡፡ ዛሬ በሚከበረው የመታሰቢያ ቀን የኢትዮጵያ ልጆች ከዳር እስከ ዳር በመነቃነቅ ጀግናው የመከላከያ ሰራዊታችን ለሀገር አንድነት እና ሠላም የከፈሉትን እጅግ መራር መስዋዕትነት እኛም በላባችን የምናፀናበት እና ደማቅ ታሪክ የምንሰራበት ሊሆን ይገባል ብለዋል፡፡

የሰላም ሚኒስቴር ሚኒስትር አቶ ብናልፍ አንዷለም በመታሰቢያ መርሃ-ግብሩ ላይ ተገኝተው ባስተላለፉት መልዕክት በበኩላቸው ዛሬ የምንዘክረው ይህ ቀን በአንድ በኩል የተፈጸመዉ ድርጊት አሳዛኝም አሳፋሪም የታሪክ አካል እንደመሆኑ ይህንን መሰል ክሕደት መቼም ቢሆን የትም ቢሆን እንዳይደገም በየዓመቱ መዘከር በማስፈለጉ ሲሆን በሌላም በኩል ለሀገሩ ዳር ድንበር ጠበቃ የኾነዉን የሀገር መከላከያ ሠራዊት መሥዋዕትነትና ጀግንነት ዕውቅና ለመስጠትና አብሮነትን ለመግለጽ ነው ብለዋል፡፡

የመከላከያ ሰራዊታችን የኢትዮጵያን ሰላም ለማረጋገጥ የሚከፍለውን መስዋዕትነት ሁሌም ክብርና አድናቆት የምንሰጠው ይሆናል ያሉት ሚኒስትሩ ሃገራዊ የሰላም ግንባታ ስራ ረዥም ጊዜንና የትውልድ ቅብብሎሽን የሚጠይቅ እንደመሆኑ መጠን በሀገራችን የነፈሰው የሰላም ተስፋ እንዲቀጥል በቀጣይ በሚኖሩ ሰላምን የማረጋገጥና የማጽናት ሥራዎች ላይ ሁሉም ኢትዮጵያዊ የበኩሉን ሚና ሊወጣ ይገባል ብለዋል፡፡

የኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ኢንጂነር ወርቁ ጋቸና በበኩላቸው በጀግና ሀገር መከላከያ ሰራዊት የደረሰው ክህደት እጅግ አሳዛኝ ክስተት ነው ብለዋል፡፡ አያይዘውም ውድ ህይወቱን ሳይሳሳ የኢትዮጵያ ልጆች ከዳር እስከዳር ያንቀሳቀሰ እንደሆነ በመጥቀስ የተከፈለውን መራር መስዋዕትነት ታሪክ የማይረሳው እንደሆነ ገልፀዋል፡፡ በመጨረሻም ኢንጂነር ወርቁ ተባብረን ከሰራን ትልቅ ህዝቦች ነን ታላቅ የሆነችውን ሀገራችንን ታላቅ አድርገን እናስቀጥላታለን ብለዋል፡፡

የፋይናንስ ደህንነት አገልግሎት ዋና ዳይሬክተር አቶ ቴዎድሮስ በቀለ በበኩላቸው ባስተላለፉት መልዕክት ጥቅምት 24/2013 ዓ/ም በሃገራችን ትልቅ ጠባሳ ያሳረፈ እለት ነው ብለዋል፡፡ ይህ ክስተት ለሀገር ውድ ዋጋ የተከፈለበት ሲሆን በዘመናት ውስጥ የማይታሰብ ክስተት እንደሆነ ገልፀዋል፡፡ አያይዘውም በዚህ መታሰቢያ ቀን ወደፊት ለትውልድ መሰል ጥቁር ጠባሳዎች እንዳይደገሙ ትልቅ ትምህርት የሚሰጥበት ነው ብለዋል፡፡

በመጨረሻም ለሃገር መከላከያ ሰራዊት አጋርነትን ለመግለጽ ያለመ በአጭር የጽሁፍ መልዕክት 6800 ላይ የአራቱ ተቋማት አመራርና አባላት ድጋፍ ያደረጉ ሲሆን የመታሰቢያ መርሃ ግብሩ በኢትዮጵያ ሕዝብ ብሔራዊ መዝሙር ተጠናቋል፡፡