"ለውጥን የማፅናት ምዕራፍ" በሚል መሪ ቃል የ2016 አዲስ አመት መቀበያ ልዩ ፕሮግራም በኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር ተካሄደ

Nested Applications

Asset Publisher

null "ለውጥን የማፅናት ምዕራፍ" በሚል መሪ ቃል የ2016 አዲስ አመት መቀበያ ልዩ ፕሮግራም በኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር ተካሄደ

"ለውጥን የማፅናት ምእራፍ" በሚል መሪ ቃል የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር (ኢመደአ) የ2015 በጀት አመት አጠቃላይ ተሃድሶ እና የ2016 አዲስ አመት መቀበያ ልዩ ፕሮግራም ጷጉሜ 2/2015 ዓ.ም ከፍተኛ የመንግስት ኃላፊዎች እና ሁሉም የአስተዳደሩ አባላት በተገኙበት በተቋሙ ቅጥር ግቢ በተለያዩ ፕሮግራሞች በደማቅ ሁኔታ ተከበረ፡፡

የኢመደአ ዋና ዳይሬክተር አቶ ሰለሞን ሶካ በፕሮግራሙ መክፈቻ ስነ ስርአት ላይ ባስተላለፉት መልእክት ሐገራዊ ለውጡን ተከትሎ ኢመደአ ሪፎርም ከተደረገባቸው የፀጥታና ደህንነት ተቋማት አንዱ መሆኑን አመላክተው ተቋሙ ያለበትን ክፍተት ለይቶ በአደረጃጀት እና መዋቅር፣ በሰው ሃይል ልማትና ስምሪት፣ ፕሮጀክት አስተዳደር እና በሌሎች ውስጣዊና ውጫዊ ሁኔታዎች ላይ አመርቂ የሚባሉ ስራዎችን በ2015 በጀት አመት መስራቱንና ተጨባጭ ስኬት ማስመዝገቡን ገልፀዋል፡፡

የሐገራችን ጥንካሬ የሚለካው እንደ የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር ባሉ የመረጃና ደህንነት ተቋማት ጥንካሬ ላይ ነው ያሉት ዋና ዳይሬክተሩ፤ ጠንካራ ተቋማት ባልተገነባበት ሐገር ጠንካራ ሀገረ መንግስት መገንባት ከባድ ነዉ ብለዋል። በመሆኑም ጠንካራ ተቋማትን የመገንባት ስራ ለነገ ተብሎ የሚተዉ ጉዳይ እንዳልሆነ ገልጸዋል።

ኢመደአ በ2015 በጀት አመት የተሳካ ሪፎርም ካከናወነባቸው ጉዳዮች መካከል አንዱ ተልዕኮን መሰረት ያደረገ የአደረጃጀትና መዋቅር ለውጥ ማድረጉ፤ እንዲሁም ለአመራርና ለሰው ሃይል ልማት ከፍተኛ ትኩረት በመስጠት አመርቂ ውጤት ማስመዝገቡ እንደሆነ አቶ ሰለሞን ሶካ ገልጸዋል፡፡ “የሰዉ ሃይላችን የስኬታችን ምንጭ ነዉ” በሚል መርህ ከፍተኛ በጀት በመመደብ የተቋሙን መካከለኛ አመራር በብሔራዊ መረጃና ደህንነት ዩኒቨርሲቲ ኮሌጅ በማሰልጠን አእምሮአዊ፣ ስነ-ልቦናዊና አካላዊ ዝግጁነትን የሚያጠናክሩ ስልጠናዎች መሰጠቱን ዋና ዳይሬክተሩ ተናግረዋል፡፡

በሌላም በኩል በሳይበር ታለንት ልማት ዘርፍም ታዳጊ ባለተሰጥኦዎችን በመመልመልና በማሰልጠን አስተዳደሩ የነገው ትውልድ ላይ ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ መሆኑን አቶ ሰለሞን ሶካ ገልጸዋል።

በ2015 በጀት ዓመት በቴክኖሎጂ ራስን ለመቻል ከፍተኛ የሚባሉ ስራዎች ለመስራት የተቻለ መሆኑን የገለጹት ዋና ዳይሬክተሩ፤ ከተቋሙ የዳታ ማዕከል ግንባታ እስከ የፒኬአይ (PKI) ፕሮጀክት፤የሃገርን ህልዉና ለመጠበቅ በመረጃ ኦፕሬሽን ላይ ከፍተኛ ስራዎችን በመስራት ለሃገር ሉዓላዊነትና ሰላም መረጋገጥ ከፍተኛ መስዋዕትነት የሚያስከፍሉ ስራዎችን መሰራቱን ዋና ዋና ዳይሬክተሩ አመላክተዋል። መጭው 2016 አዲስ አመት ለኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር አመራርና አባላት እንዲሁም ለመላው ኢትዮጵያዊያን የሰላም፣ የፍቅር፣ የብልፅግና፣ የመተሳሰብ ዓመት እንዲሆን መልካም ምኞታቸውን ገልፀዋል፡፡

የ2015 በጀት አመት አጠቃላይ ተሃድሶ እና የ2016 አዲስ አመት መቀበያን ምክንያት በማድረግ በተዘጋጀው መርሃ ግብር ላይ በ2015 በጀት አመት የተሻለ አፈጻጸም ላስመዘገቡ የአስተዳደሩ አባላት እውቅና የተሰጠ ሲሆን፤ በተመሳሳይ የተቋሙ የሪፎርም ስራ ኮሚቴ በመሆን ከፍተኛ አስተዋፆ ላበረከቱ አመራርና አባላትም እውቅና ተሰጥቷል፡፡

በሌላም በኩል ጷጉሜ 1 ቀን 2015 ዓ.ም የተከበረውን የአገልጋይነት ቀን በማስመልከት ከ38 ዓመት በላይ በተቋሙና በሌሎች መንግስታዊ ተቋማት ላይ ሐገራቸውን ያገለገሉ 5 (አምስት) የኢመደአ አባላት ምስጋናና እውቅና ተሰጥቷቸዋል፡፡

በመጨረሻም ለበርካታ አመታት በኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር ሲያገለግሉ ለቆዩና ወደ ሌሎች የመንግስት ተቋማት በሃላፊነት ለተመደቡ የቀድሞ የአስተዳደሩ አባላት የሽኝት መርሃ ግብር በማድረግ የፕሮግራሙ ፍጻሜ ሆኗል፡፡