4ኛው የሳይበር ደህንነት ወር ከጥቅምት 1/2016 እስከ ጥቅምት 30/2016 ዓ.ም ድረስ ይከበራል

[#if smallImage??]
    [#if smallImage?is_hash]
        [#if smallImage.alt??]
            ${smallImage.alt}
        [/#if]
    [/#if]
[/#if]

የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር (ኢመደአ) ዋና ዳይሬክተር አቶ ሰለሞን ሶካ ከጥቅምት 1-30/2016 ዓ.ም ድረስ የሚከበረውን 4ኛውን ብሔራዊ የሳይበር ደህንነት ወር አስመልክቶ ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጡ፡፡

ዋና ዳይሬክተሩ በመግለጫቸው 4ኛው የሳይበር ደህንነት ወር “አይበገሬ የሳይበር አቅም ለሀገር ሉዓላዊነት - Resilient Cyber Capability for National Sovereignty” በሚል መሪ ቃል በተለያዩ የግንዛቤ ማስጨበጫ መርሐ ግብሮች እንደሚከበር ገልጸዋል፡፡

በሃገራችን 4ኛው የሳይበር ደህንነት ወር መከበር ዋና ዓላማ የሳይበር ማህበረሰቡንና የተቋማትን የሳይበር ደህንነት ንቃተ ሕሊና ለማጎልበት የሚያስችል ንቅናቄ በመፍጠር የሃገራችንን የብሔራዊ ጥቅሞችን የማስጠበቅ ተልዕኮን ማገዝ ነው ብለዋል፡፡ በተጨማሪም የተቋማትን የሳይበር ደህንነት ዝግጁነት ማሻሻል፣ የሳይበር ደህንነት ጥናትና ምርምሮችን ማበረታታት፣ እና የሳይበር ደህንነትና ተያያዥ መስክ የተሰማሩትን የግሉን ዘርፍ ማነቃቃት የሳይበር ደህንነት ወር ዝርዝር ዓላማዎች እንደሆነ ዋና ዳይሬክተሩ በመግለጫቸው አብራርተዋል፡፡

የሳይበር ደህንነት ወር በዓለም አቀፍ ደረጃ ለ20ኛ ጊዜ እንደሚከበርና ሃገራት የዜጎቻቸውን ብሎም የተቋሞቻቸውን የሳይበር ደህንነት ንቃተ ሕሊና ለማሳደግ የሚያስችል የሳይበር ደህንነት የግንዛቤ ማስጨበጫ መርሃ ግብሮችን በማከናወን እንደሚያከብሩ ዋና ዳይሬክተሩ ገልጸዋል፡፡

የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር የሳይበር ደህንነት ማስጠበቂያ ፖሊሲዎች፣ የህግ ማዕቀፎች፣ ስታንዳርድ እና መመሪያዎች በማርቀቅ የመሪነትን ሚናውን ቢወስድም በኢንዱስትሪው የተሰማሩ የግል እና የመንግስት ተቋማት በቅንጅት ከመስራትና ብሔራዊ አቅም ከመፍጠር አንጻር፣ የቴክኖሎጂ ባለቤትነትን ከማረጋገጥ እና የሳይበር ደህንነትን እውን ከማድረግ እንዲሁም በሳይበር ደህንነት ዘርፍ የሚካሄዱ ጥናትና ምርምሮችን በማበረታታት የሳይበር ደህንነት ሉዓላዊነትን ማረጋገጥ ወሳኝ እንደሆነ አቶ ሰለሞን ሶካ ገልጸዋል፡፡

በ3ኛው ብሔራዊ የሳይበር ደህንነት ወር በተፈጠረው ንቅናቄና ልዩ ልዩ መርሃ ግብሮች በአጠቃላይ ወደ 50 ሚሊየን የሚጠጉ ዜጎችን መድረስ እንደተቻለ እና በዘንድሮም ከዚህ የማይተናነስ የህብረተሰብ ክፍልን ለመድረስ በተለያዩ ሚዲያዎች እንደሚሰራ ዋና ዳይሬክተሩ ገልጸው ለዚህም የመክፈቻ ፕሮግራሙን ጨምሮ ሌሎች መርሃ ግብሮች በአስተዳደሩ የማህበራዊ ሚዲያ አማራጮች የቀጥታ ስርጭት (Live Streaming) ሽፋን እንደሚያገኙ አስረድተዋል፡፡

4ኛው ሃገር አቀፍ የሳይበር ደህንነት ወር የመክፈቻ ፕሮግራም እንዲሁም የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር የሀገራችንን የሳይበር ደህንነት ለማረጋጋጥ የሚያደርገውን የሳይበር ውጊያ የሚያስቃኝ በእውነተኛ ሁነቶች ላይ ተመስርቶ የተሰራ “ሥውር ውጊያ” የተሰኘ ፊልም ምርቃት እሁድ ጥቅምት 4/2016 ዓ.ም በኢትዩጵያ ንግድ ባንክ ዋና መ/ቤት አዳራሽ ከፍተኛ የመንግስት ባለስልጣናት፣ የውጭ ሀገራት አምባሳደሮች እና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች በተገኙበት የሚካሄድ እንደሆነ አቶ ሰለሞን ገልጸዋል፡፡

4ተኛው ሃገር አቀፍ የሳይበር ደህንነት ወር በአምስት (5) ዋና ዋና መርሃ ግብሮችን እንደሚከበር የገለጹት ዋና ዳይሬክተሩ፤ በዚህም ጥቅምት 04/2016 ዓ.ም የሚካሄደው የመክፈቻ እና የፊልም ምረቃ መርሃ ግብር፣ ጥቅምት 12/2016 ዓ.ም የሚካሄድ ብሄራዊ የሳይበር ደህንት ስጋት ጥናት ላይ ያተኮረ የፓናል ውይይት፣ ጥቅምት 19/2016 ዓ.ም የብሔራዊ የሳይበር ደህንነት ንቃተ ህሊና ጥናት ውጤት ላይ የሚካሄድ ውይይት፣ ጥቅምት 22/2016 ዓ.ም በሳይበር ፖሊሲና ስታንዳርድ ዙሪያ የሚደረግ ቨርችዋል ውይይት፣ እና ጥቅምት 29/2016 ዓ.ም የሚካሄድ ሃገራዊ የሳይበር ደህንነት የምርምር ኮንፈረንስ መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡ ከላይ ከሚካሄዱት ልዩ ልዩ መድረኮች በተጨማሪ ኢመደአ እና በሳይበር ደህንነት እና ተያያዥ ዘርፎች ላይ የተሰማሩ ሃገር በቀል የግል ድርጅቶች ምርትና አገልግሎታቸውን በአውደ ርዕይ መልክ የሚያሳዩበት ከጥቅምት 12/2016 ዓ.ም እስከ ጥቅምት 15/2016 ዓ.ም ድረስ በግዮን ሆቴል ክፍት ሆኖ የሚቆይ ኤግዚቢሽን እንደሚኖር አቶ ሰለሞን ሶካ ገልጸዋል፡፡

የሳይበር ወሩ በተለያዩ የሳይበር ደህንነት የንቃተ ህሊና ማሳደጊያ ኮንፍረንሶች፣ መድረኮች እና አውደ ርዕይ ሁሉም የማህበረሰብ ክፍሎች እና ተቋማትን በማሳተፍ መልኩ የሚከበር ይሆናል ያሉት አቶ ሰለሞን ሶካ ሕብረተሰቡም በሚካሄዱት መድረኮች እንዲሁም ዓውደ ርዕዩን በመጎብኘት የነቃ ተስዳትፎ እንዲያደርግና የሳይበር ደህንነት ንቃተ ሕሊናውን እንዲያጎለብት ጥሪያቸውን አስተላልፈዋል፡፡

Asset Publisher


የቅርብ ዜናዎች