3ኛው ሃገር አቀፍ የሳይበር ደህንነት ወር በስኬት መጠናቀቁን አስመልክቶ የእውቅናና የምስጋና መርሃ ግብር ተካሄደ
3ኛው ሃገር አቀፍ የሳይበር ደህንነት ወር በስኬት መጠናቀቁን አስመልክቶ የእውቅናና የምስጋና መርሃ ግብር ተካሄደ
“የተቀናጀ የሳይበር ደህንነት ለሃገር ሉዓላዊነት” በሚል መሪ ቃል ከጥቅምት 1 – 30/2015 ዓ/ም የተካሄደው 3ኛው ሃገር አቀፍ የሳይበር ደህንነት ወር በስኬት መጠናቀቁን አስመልክቶ ለመርሃ ግብሩ ስኬት በስትራቴጂክ አጋርነት ለተሳተፉ እንዲሁም በተለያየ መልኩ ድጋፍ ላደረጉ አካላት የእውቅናና የምስጋና መርሃ ግብር ተካሄደ፡፡
በእውቅናና የምስጋና መርሃ ግብሩ ላይ ተገኝተው ንግግር ያደረጉት የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር (ኢመደአ) ዋና ዳይሬክተር የተከበሩ አቶ ሰለሞን ሶካ እንደገለጹት ለመርሃ ግብሩ መሳካት ቁልፉ ጉዳይ በመደመር እሳቤ ከተለያዩ ተቋማትና ባለድርሻ አካላት ጋር በቅንጅት መሰራት መቻሉ ነው ብለዋል፡፡ በዚህም የሳይበር ደህንነት ጉዳይን የጋራ ሃላፊነት እንደሆነ በመገንዘብ በ3ኛው የሳይበር ደህንነት ወር ላይ በስትራቴጂክ አጋርነት፣ በአጋርነት እንዲሁም በተለያየ መልኩ አስተዋጻኦ ላደረጉ ተቋማት እና ግለሰቦች በአስተዳደሩ ሥም ላቅ ያለ ምስጋናቸውን አቶ ሰለሞን ሶካ አቅርበዋል፡፡
በ3ኛው የሳይበር ደህንነት ወር ከተካሄዱ አጠቃላይ መርሃ ግብሮች ውስጥ ኢመደአ 30 በመቶውን ድርሻ ብቻ እንደወሰደ የገለጹት ዋና ዳይሬክተሩ ቀሪውን 70 በመቶ ድርሻ በዘርፉ የተሰማሩ የግልና የመንግስት ተቋማት በተለያየ መልኩ፤ ዓውደ ርዕይ በማቅረብ፣ የፓናል ውይይቶች ላይ በመሳተፍ እንዲሁም መርሃ ግብሩን በፋይናንስ በመደገፍ ከፍተኛውን ድርሻ እንደወሰዱ አብራርተዋል፡፡
ሃገራዊ የሳይበር ደህንነት ጉዳይ የሁሉም ተቋማትና ባለድርሻ አካላት የጋራ ጉዳይ እንደመሆኑ መጠን በ3ኛው የሳይበር ደህንነት ወር ላይ የታየው የቅንጅትና የትብብር ሥራ በቀጣይም ተጠናክሮ መቀጠል እንደሚገባው ዋና ዳይሬክተሩ መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡
3ኛውን የሳይበር ደህንነት ወር በስትራቴጂክ አጋርነት የደገፉ ተቋማት የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ፣ ኢትዮ ቴሌኮም፣ ፣ አቢሲኒያ ባንክ እና የኦሮሚያ ሕብረት ሥራ ባንክ ሲሆኑ አዋሽ ባንክ ፣ ዳሽን ባንክ፣ ዳን ኢነርጂስ፣ ቼክ ፖይንት፣ ዴሊቨር አይሲቲ፣ የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ሃይል ፣ ብርሃን ባንክ፣ አይፒ ኮም ቴክኖሎጂስ ትሬዲንግ ፣ አትላስ ኮምፒዉተር ቴክኖሎጂ እና ሁዋዊ ኢትዮጵያ በአጋርነት ተሳትፈዋል፡፡