የኢትዮ ሳይበር ታለንት ልማት ማዕከል በሳይበር ደህንነት ዘርፍ ብቁ የሰው ሀይል ለማፍራት እየሰራ መሆኑ ተገለጸ

[#if smallImage??]
    [#if smallImage?is_hash]
        [#if smallImage.alt??]
            ${smallImage.alt}
        [/#if]
    [/#if]
[/#if]

የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር (ኢመደአ) “የኢትዮ ሳይበር ታለንት ልማት ማዕከል” በ2015 በጀት አመት 9 ወራት ውስጥ በተለያየ የእድሜ ክልል የሚገኙ 120 የሚሆኑ ታዳጊ ወጣቶችን በመደበኛ፣ በቅዳሜና እሁድ እንዲሁም በክረምት /Summer/ ፕሮግራም ተሳታፊ ማድረጉን የማዕከሉ ሃላፊ አቶ ካሳሁን ደሳለኝ ገለጹ፡፡

አቶ ካሳሁን አያይዘው እንደገለጹት አለም እየተመራች ካለችበት እጅግ ተለዋዋጭና ውስብስብ የሳይበር ምህዳር አንፃር በሳይበር ደህንነት መስክ ልዩ ተሰጥኦ ያላቸውን ታዳጊ ወጣቶች በየደረጃው ማነቃቃት፣ መመልመል፣ ማልማትና መጠቀም አማራጭ የሌለው ጉዳይ ነው ብለዋል ። ስለሆነም ታዳጊዎች እና ወጣቶች በሳይበር ደህንነት እና ተያያዥ ዘርፎች ያላቸውን እምቅ አቅም ወጥ በሆነ እንዲሁም ሳይንሳዊ፣ አውዳዊና ተለዋዋጭ /dynamic/ በሆኑ ዘዴዎች መለየት፣ መመልመል፣ ማልማትና መጠቀም ወሳኝ ጉዳይ እንደሆነም አንስተዋል፡፡

ባለ ልዩ ተሰጥኦ ታዳጊዎች ወደ ማእከሉ እንዲገቡ የሚቀርቡ የመመልመለያ መስፈርቶች እንደየ ዕድሜና የትምህርት ዝግጅታቸው የተለያየ ሲሆን ከመደበኛ ትምህርታቸው ጎን ለጎን ራሳቸውን እያስተማሩ ያካበቱትን ክህሎት እና ሊሰሩ ያሰቡትን ፕሮጀክት ፕሮፖዛል በማቅረብ እንደሆነ አቶ ካሳሁን ገልጸዋል፡፡

አስተዳደሩ በምልመላ ያገኛቸውን እና መመዘኛውን ያለፉ ሰልጣኞችን ወደ ማዕከሉ ሲቀላቀሉ የቴክኒካል እና አስተሳሰብ (mindset) ድጋፍ የሚያደርጉ ባለሙያዎችን በመመደብ፣ የስራ ከባቢያቸውን ምቹ በማድረግ በተጨማሪ ለሚሰሯቸው ስራዎች መስሪያ ቁሳቁሶችን ድጋፍ እንደሚያደር አቶ ካሳሁን ተናግረዋል፡፡

የኢመደአ “የኢትዮ ሳይበር ታለንት ልማት ማዕከል” በ2015 በጀት አመት ለመጀመሪያ ጊዜ 62 ሰልጣኞችን በክረምት ፕሮግራም (Summer Program) አሰልጥኖ ያስመረቀ ሲሆን ሰልጣኞችም እንደየችሎታቸውና እንደስራዎቻቸው ከተለያዩ ባለሀብቶች ጋር የማስተሳሰር ስራም መሰራቱን አቶ ካሳሁን ተናግረዋል፡፡ በቀጣይም “የኢትዮ ሳይበር ታለንት ልማት ማዕከል” በሃገር አቀፍ ደረጃ የልህቀት ማዕከል (Excellence Center) በመሆን በዘርፉ ብቁ ባለሙያዎችን እያፈራ እንደ ሀገር በዘርፉ ያለውን የባለሙያ እጥረት ለመሸፈን ልዩ ተሰጥኦ ያላቸው ታዳጊ ወጣቶችን ከትምህርታቸው ጎን ለጎን ክህሎቶቻቸውን የሚያሳድጉበት ከባቢ ለመፍጠር እየሰራ እንደሚገኝ አቶ ካሳሁን ገልጸዋል፡፡

በሳይበር ደህንነት እና ተያያዥ ዘርፎች ልዩ ችሎታ ያላቸው እና የመመዝገቢያ መስፈርቱን የሚያሟሉ ታዳጊዎች እና ወጣቶች በማእከሉ ለመመዝብ እና መረጃዎችን ለማግኘት የማዕከሉን የድረ-ገጽ አድራሻ https://cychallenge.insa.gov.et በመጎብኘት ተጨማሪ መረጃ ማግኘትና መመዝገብ እንደሚችሉ አቶ ካሳሁን መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል::