የሳይበር ዘርፉን ለማሳደግ የሴቶች ሚና ከፍተኛ መሆኑ ተገለጸ

[#if smallImage??]
    [#if smallImage?is_hash]
        [#if smallImage.alt??]
            ${smallImage.alt}
        [/#if]
    [/#if]
[/#if]

 

ብሔራዊ የሳይበር ደህንነትን ለማረጋገጥ የሴቶች ተሳትፎና ሚና ወሳኝ መሆኑን የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር (ኢመደአ) ዋና ዳይሬክተር ዶ/ር ሹመቴ ግዛው ገለጹ፡፡

“እኔም የእህቴ ጠባቂ ነኝ” በሚል መሪ ቃል ዓለም አቀፉ የሴቶች ቀን በተለያዩ ዝግጅቶች በኢመደአ ተከብሯል፡፡

በዕለቱ ተገኝተው መልዕክት ያስተላለፉት ዶ/ር ሹመቴ፤ ሴቶች ወደ አመራርነት እንዲመጡና የሳይበር ዘርፉን ለማሳደግ ተሳትፎ እንዲያደርጉ ሁላችንም ድርሻችንን መወጣት ይጠበቅብናል ብለዋል፡፡

ዋና ዳይሬክተሩ አክለውም በዓለም አቀፍ ደረጃ የሴቶች ቀን እንዲከበር ካስገደዱ ምክንያቶች መካከል የፍትህ መጓደልና የምግብ ዋስትና አለመረጋገጥ በመኖሩ ምክንያት መሆኑን አስታውሰው በሃገራችንም በሴቶች ላይ የሚደርሱ ችግሮችን ለመቅረፍ የሁሉም ዜጋ ርብርብ ሊኖር ይገባል ብለዋል፡፡

በበዓሉ ላይ የተገኙት የኢመደአ ም/ዋና ዳይሬክተሮች ዶ/ር አንተነህ ተስፋየ እና የተከበሩ አቶ ሰለሞን ሶካ የየበኩላቸውን መልዕክት ያስተላለፉ ሲሆን ሴቶችን የማብቃትና የሳይበር ዘርፉን እንዲመሩ የማስቻሉ ሂደት የሁሉም ሃላፊነት መሆኑን በማስታወስ እንደ ተቋም የአስተዳደሩን የሴቶችና ሕጻናት ዳይሬክቶሬት ሥራዎች መደገፍ እንደሚገባ ገልጸዋል፡፡

የኢመደአ የሴቶች፣ ሕጻናትና ወጣቶች ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር ወ/ሪት የምስራች ፋሪስ በበኩላቸው በኢመደአ ውስጥ በርካታ ሴት ጀግኒቶች እንዳሉ ገልጸው ለእነዚህ ጀግኒቶች ተገቢውን ክብር መስጠትና ሌሎች ጀግኒቶች እንዲበረታቱ ምቹ መደላድል መፍጠር እንደሚገባ አስገንዝበዋል፡፡

ሴቶች እድሉን ካገኙ ማሳካት የማይችሉት የለም ያሉት ዳይሬክተሯ፤ ለዚህ ደግሞ የወንዶች እገዛ ወሳኝ መሆኑ ተናግረዋል፡፡ በዕለቱም የዳይሬክቶሬቱን ሥራዎች በመደገፍ አስተዋጻኦ ላደረጉ አካላት እውቅና ተሰጥቷል፡፡

ዓለም አቀፍ የሴቶች ቀን በዓለም አቀፍ ደረጃ ለ111ኛ ጊዜ በሃገራችን ደግሞ ለ46ኛ ጊዜ “እኔም የእህቴ ጠባቂ ነኝ” በሚል መሪ ቃል ታስቦ ዉሏል።