በሳይበር ደህንነት እና ሉዓላዊነት ዙሪያ የሚወጡ ሕጎችና ፖሊሲዎች ተገቢውን ትኩረት እንዲያገኙ የሕዝብ ተወካዮች እና የፌዴሬሽን ም/ቤቶች በትኩረት ሊሰሩ ይገባል፡ የተከበሩ አቶ አገኘሁ ተሻገር፡ የፌዴሬሽን ም/ቤት አፈጉባኤ

[#if smallImage??]
    [#if smallImage?is_hash]
        [#if smallImage.alt??]
            ${smallImage.alt}
        [/#if]
    [/#if]
[/#if]

"የተቀናጀ የሳይበር ደህንነት ለሃገር ሉዓላዊነት" በሚል መሪ ቃል ከጥቅምት 1/2015 እስከ ጥቅምት 30/2015 ዓ/ም ድረስ እየተካሄደ የሚገኘው 3ኛው ሃገር አቀፍ የሳይበር ደህንነት ወር የ4ኛ ሳምንት መርሃ ግብር በሳይንስ ሙዚየም በመካሄድ ላይ ይገኛል፡፡

የ4ኛ ሳምንት የሳይበር ደህንነት ወር መርሃ ግብር የማህበረሰብ አቀፍ የግንዛቤ ማስጨበጫ ሲሆን በዚህም የዜጎችን እና የተቋማትን የሳይበር ደህንነት ግንዛቤ በማሳደግና ባህል በመገንባት ረገድ ቀጣይነት ያለው የግንዛቤ ማስጨበጫ ሥራዎች የሚሰራበት ሳምንት ነው፡፡

በሌላም በኩል የሃገራችን ከፍተኛ የሥልጣን እርከን አካል የሆኑት የሕዝብ ተወካዮች እና የፌዴሬሽን ም/ቤቶች የሃገራችንን የሳይበር ደህንነት በማረጋገጥ እና ዲጂታል ሉዓላዊነታችንን በማረጋገጥ ረገድ የሚሰሩ ሥራዎችን፤ የቴክኖሎጂ ልማት፣ የሰው ሃይል ልማት፣ እንዲሁም የአሰራር ስርአት መዘርጋት ላይ የተሰሩ ሥራዎችን በጉልህ እንዲገነዘቡ ለማድረግ የሚያስችል ገለጻ እና በቀጣይም ሃገራዊ የሳይበር ደህንነት በማረጋገጥ በኩል ሊሰሩ የሚገቡ ሥራዎች ዙሪያ ውይይት የሚደረግ ይሆናል፡፡

በ4ኛ ሳምንት የሳይበር ደህንነት ወር መርሃ ግብር ላይ በክብር እንግድነት ተገኝተው ንግግር ያደረጉት የፌዴሬሽን ም/ቤት አፈጉባኤ የተከበሩ አቶ አገኘሁ ተሻገር ባስተላለፉት መልዕክት የህግ አውጪው፤ የሕግ ተርጓሚውና አስፈጻሚው አካል በሳይበር ደህንነት እና ሉዓላዊነት ዙሪያ የሚወጡ ሕጎችና ፖሊሲዎች ተገቢውን ትኩረት እንዲያገኙ በትኩረት ሊሰራ ይገባል ብለዋል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ የም/ቤቱ ቋሚ ኮሚቴዎች የሚከታተሏቸውና የሚቆጣጠሯቸው ተቋማትም የሳይበር ደህንነት ጉዳይን ስትራቴጂክ ተቋማዊ ጉዳያቸው አድርገው እንዲመሩ ማስገንዘብ ይኖርባቸዋል ብለዋል።

አፈጉባኤ የተከበሩ አቶ አገኘሁ ተሻገር ባደረጉት ንግግር ካነሷቸው ዋና ዋና ነጥቦች መካከል፤

• ለሃገራችን ብልፅግና መረጋገጥ ወሳኝ ሚና ከሚኖራቸው ዘርፎች መካከል ቴክኖሎጂ አንዱ በመሆኑ መንግስት ከአስር አመቱ የልማት ዕቅዶች መካከል አንዱ በማድረግ ትኩረት ሰጥቶ በመስራት ላይ ይገኛል፡፡

• በሳይበር ምህዳሩ ውስጥ ወሳኝ ሚና ለሚጫወተው የሰው ሀይል ልማት ተገቢው ትኩረት ሊሰጥ ይገባል፡፡ ለዚህም በየደረጃው ተሰጥኦ ላላቸው ታዳጊዎች እየተሰጠ ያለው ድጋፍ እና ማበረታቻ በሁሉም ባለድርሻ አካላት ተጠናክሮ መቀጠል ይኖርበታል፡፡

• የሳይበር ደህንነት የማስጠበቅ ስራችን ካለ ማህበረሰቡ ተሳትፎ በአንድ እጅ ማጨብጨብ ስለሚሆን በኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር ተዘጋጅቶ በየአመቱ ጥቅምት ወር የሚከበረው መድረክ በአይነቱም ሆነ በተደራሽነቱ መጎልበት ይኖርበታል፡፡

• የበጀትና የፖለቲካ ውሳኔ ሰጪ የሆኑ አካላት የዘርፉን አስፈላጊነት በመረዳት በየደረጃው ለሰው ሀይል፣ ለቴክኖሎጂ ልማት እና የአሰራር ስርአትን በመዘርጋት ተገቢውን ትኩረት እንዲሰጡ ማድረግ ይገባል፡፡

• የሳይበር ቴክኖሎጂ ለሀገራችን አዲስ እንደመሆኑና በርካታ የሰለጠነ የሰው ሀይል የሚፈልግ እንደመሆኑ መጠን የሀገራችን ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት በዘርፉ ያለውን የሠው ሀይል እጥረት ለመቅረፍ ብሎም ተወዳዳሪ አለም አቀፍ አቅም መፍጠር ይቻል ዘንድ ከወዲሁ ትኩረት ሰጥተው መስራት ይኖርባቸዋል፡፡

• በራስ አቅም የለሙ እና ወረቀት አልባ ስርዓትን ለመዘርጋት በሚደረገው ጥረት ላይ አቅም የሚሆኑ ቴክኖሎጂዎችን በመጠቀም ረገድ እንደ ህዝብ ተወካይነታችን የመሪውን ሚና መውስድ አለብን፡፡