የኢመደአ ዋና ዳይሬክተር የ2016 አዲስ ዓመትን በማስመልከት የእንኳን አደረሳችሁ መልዕክት አስተላለፉ የኢመደአ ዋና ዳይሬክተር አቶ ሰለሞን ሶካ በኢትዮጵያ የተባበሩት አረብ ኢሚሬትስ ኤምባሲ የፖለቲካ፣ ኢኮኖሚና የሚዲያ ጉዳዮች ሃላፊ ታላል አል አዘሪ ጋር ተወያዩ
Nested Applications
Asset Publisher
የኢመደአ ዋና ዳይሬክተር አቶ ሰለሞን ሶካ በኢትዮጵያ የተባበሩት አረብ ኢሚሬትስ ኤምባሲ የፖለቲካ፣ ኢኮኖሚና የሚዲያ ጉዳዮች ሃላፊ ታላል አል አዘሪ ጋር ተወያዩ
የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር (ኢመደአ) ዋና ዳይሬክተር አቶ ሰለሞን ሶካ በኢትዮጵያ የተባበሩት አረብ ኢሚሬትስ ኤምባሲ የፖለቲካ፣ ኢኮኖሚና የሚዲያ ጉዳዮች ሃላፊ ከሆኑት ታላል አል አዘሪ ጋር በሳይበር ደህንነት እና ተያያዥ ጉዳዮች ዙሪያ ውይይት አካሄዱ፡፡
በዉይይቱም የሳይበር ቴክኖሎጂ ባለቤትነትን በማረጋገጥና በዘርፉ ያለዉን የሰዉ ሃይል እጥረት በመቅረፍ ረገድ በጋራና በትብብር መስራት በሚቻልባቸው ጉዳዮች ዙሪያ መክረዋል፡፡
ኢመደአ የኢትዮጵያን የሳይበር የቴክኖሎጂ ባለቤትነትን ለማረጋገጥ እየሰራ ያለዉ ስራ ለሌሎች አፍሪካ አገራት ምሳሌ ሊሆን የሚችል መሆናቸዉን የጠቀሱት ታላል አል አዘሪ ይህ መልካም ተሞክሮ ወደ ሌሎች አፍሪካ አገራት መስፋት የሚገባዉ መሆኑን ገልጸዋል። አያይዘውም በኢትዮጵያ የተባበሩት አረብ ኢሚሬትስ ኤምባሲ ከኢመደአ ጋር በሳይበር ደህንነት ዘርፍ በይበልጥ በታዳጊዎች የሳይበር ታለንት ልማት ላይ በትብብር መስራት ፍላጎት እንዳለዉ ሚስተር ታላል ገልጸዋል።
የኢመደአ ዋና ዳይሬክተር አቶ ሰለሞን ሶካ በበኩላቸው ኢመደአ በሳይበር ቴክኖሎጂ ባለቤትነት እንዲሁም በሳይበር ታለንት ልማት ያካበተውን ተሞክሮ ለሌሎች የአፍሪካ ሐገራት ለማካፈል ዝግጁ መሆኑን ገልጸዋል።
አቶ ሰለሞን ሶካ ከታላል አል አዘሪ ጋር ካደረጉት ውውይት ባሻገር ኢመደአ ሐገራዊ የቴክኖሎጂ እና የእውቀት ባለቤትነትን በማረጋገጥ ረገድ እየሰራቸው የሚገኙ ሥራዎችን፤ የኢትዮ ሳይበር ታለንት ልማት ማዕከልን፤ እና ሌሎች ተቋማዊ ምርትና አገልግሎቶችን አስጎብኝተዋቸዋል፡፡
Asset Publisher
የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር (ኢመደአ) ዋና ዳይሬክተር የተከበሩ አቶ ሰለሞን ሶካ ለተቋሙ ማህበረሰብ እና ለመላው ኢትዮጵያዊያን የ2016 አዲስ አመትን በማስመልከት የእንኳን አደረሳችሁ መልዕክት አስተላልፈዋል።
በአዲስ ዓመት መልዕክታቸዉ፤ ያለፈዉ 2015 ዓመት በስኬትና በተግዳሮት የታጀበ ነበር ያሉት ዋና ዳይሬክተሩ ከስኬቶቻችን መካከል በሰሜኑ የአገራችን ክፍል የነበረዉ ጦርነት በእርቅ የተቋጨበት፣ የአራተኛዉ ዙር የታላቁ የህዳሴ ግድብ የዉሃ ሙሌት በስኬት የተጠናቀቀበት፣ አገራዊ ግዙፍ ፕሮጀክቶችን በመፍጠንና በመፍጠር እሳቤ በአጭር ጊዜ በማጠናቀቅ የይቻላል መንፈስ የተፈጠረበት ዓመት እንደነበር ገልጸዋል።
በተቋም ደረጃ በ2015 ዓ.ም በለዉጥ ዉስጥ ከፍተኛ የሚባሉ ስራዎች መሰራታቸዉን ያወሱት የኢመደአ ዋና ዳይሬክተር አቶ ሰለሞን በተገባደደዉ ዓመት በይፋዊ የህዝብ መሰረተ ልማት/PKI ግንባታ ፣ በአገራችን በሳይበር ጥቃት ሊደርስ የነበርን ከ23 ቢሊዮን ብር በላይ ግምታዊ ዋጋ ያለዉን ኪሳራ በማስቀረት ረገድ ፣ በአገር አቀፍ ደረጃ በዘርፉ ያለዉን የሰዉ ሀይል እጥረት ለመቅረፍና የቴክኖሎጂ ባለቤትነትን ለማረጋገጥ ባለ ልዩ ተሰጥዎ ታዳጊዎችን በማሰልጠንና በማስመረቅ ደረጃ ስኬታማ ዓመት እንደነበር ገልጸዋል።
በሌላ መልኩ አገራችን ባገባደድነው 2015 ዓ.ም በብዙ መልኩ በዉስጥም በዉጭም የተፈተነችበት ዓመት መሆኑን ያነሱት ዋና ዳይሬክተሩ ጠላቶቻችን የተለያዩ የሳይበር ጥቃቶችን በአይነትና በስፋት በመጨመር እንዲሁም የዲጂታል ሚዲያዎችን በመጠቀም የሀሰት መረጃዎችን በማሰራጨት ከፍተኛ የሚባል የስነልቦና ጦርነት የከፈቱበት ዓመት እንደነበር ዋና ዳይሬክተሩ ተናግረዋል።
የገጠሙንን ተግዳሮቶች እንደ አገር ችግሮችን የማለፍ እሴቶቻችንን በመጠቀም፣ ከሌሎች የጸጥታና ደህንነት ተቋማት ጋር በጋራ በመሆን አገራችን እንድትጸና የማድረግ ስራዎች ተሰርተዋል ያሉት አቶ ሰለሞን በተቋም ደረጃ የገጠሙንን ችግሮች ደግሞ በጥብቅ ዲስፕሊን፣ በሙያዊ ልህቀትና የአገር ፍቅር ስሜት እየተሻገርን እዚህ ደርሰናል ብለዋል።
ኢመደአ በአዲሱ ዓመት አገራዊ ፋይዳቸው ላቅ ያሉ ተግባራት ማለትም የሳይበር ሉዓላዊነት በሚያስጠብቁ ዘርፎች፣ የቴክኖሎጂ ባለቤትነት የሚያረጋግጡ ስራዎች ላይ ትኩረት በማድረግ፣ አገራዊ ልማትን የመደገፍ፣ የአገረ መንግስት ግንባታ ሂደትን የማሳለጥና ኢትዮጵያን የማጽናት ስራ ላይ ተቋማዊ ሃላፊነታችንን እንወጣለን ብለዋል።
በአዲሱ ዓመት መላው ኢትዮጵያውያን ቀድሞ የነበረንን የመረዳዳትና የመተዛዘን ባህል በማስቀጠል ለተቸገሩና የኢኮኖሚ አቅማቸው ዝቅተኛ ለሆኑ የሕብረተሰብ ክፍሎች ያለንን በማካፈል በዓሉን በአንድነት፣ በደስታና በፍቅር ማክበር እንደሚገባ ዋና ዳይሬክተሩ ጠቁመዋል።
በመጨረሻም መጪው 2016 አዲስ ዓመት ለኢመደአ ማህበረሰብ እና ለመላዉ ኢትዮጵያዊያን የሰላም ፣የፍቅር ፣ የብልፅግና የመተሳሰብ እንዲሆን የመልካም ምኞት መልዕክታቸዉን አስተላልፈዋል።