ኢትዮጵያ ዓለም አቀፉን የበይነ መረብ አስተዳደር ጉባኤ ከህዳር 19 እስከ 23/2015 ዓ.ም ድረስ ታስተናግዳለች
ኢትዮጵያ ዓለም አቀፉን የበይነ መረብ አስተዳደር ጉባኤ ከህዳር 19 እስከ 23/2015 ዓ.ም ድረስ ታስተናግዳለች
ኢትዮጵያ ከህዳር 19 እስከ 23/2015 ዓ.ም ድረስ ለ17ኛ ጊዜ የሚካሄደውን ዓለም አቀፉን የበይነ መረብ አስተዳደር ጉባኤ ታስተናግዳለች::
ኢትዮጵያ በምታስተናግደው ዓለም አቀፉ የበይነ መረብ አስተዳደር ጉባኤ ላይ በይነ-መረብን የተሻሻለ፣ ደህንነቱ የተጠበቀ፣ ተደራሽ የሆነና ተመጣጣኝ ለማድረግ በሚቻልባቸው ጉዳዮች ላይ ምክክር ይደረጋል።
በጉባኤው ላይ ከተለያዩ የአለም ሀገራት የተውጣጡ ከ2ሺ እስከ 2ሺ 500 የሚደርሱ ተሳታፊዎች እንደሚታደሙበት ይጠበቃል፡፡
ዓለም አቀፉ የበይነ-መረብ አስተዳደር ጉባኤ/መድረክ በተባበሩት መንግስታት ድርጅት ዋና ጸሐፊ አማካኝነት እኤአ በ2006 ዓ/ም ይፋ የተደረገ ፎረም ነው፡፡ የዚህ ጉባኤ ዋና አላማም የተለያዩ ተሳታፊዎችንና ባለድርሻ አካላትን በአንድ መድረክ ላይ በማምጣት ከበይነ-መረብ አስተዳደር ጋር የተያያዙ ፖሊሲዎች ላይ ውይይት የሚካሄድበት መድረክ ነው፡፡
ይህ በየዓመቱ በሚካሄደው ፎረም ላይ ከተለያዩ ሀገራትና ዘርፍ የተውጣጡ ተወካዮች የሚወያዩበት፣ መረጃ የሚለዋወጡበትና ልምድ የሚቀስሙበት ነው፡፡ የበይነ-መረብ አስተዳደር ፎረም ከበይነ-መረብ ጋር ተያይዞ ያሉ ዕድሎችን እንዲሁም ፈተናዎችና ተግዳሮቶችን በተመለከተ የሚነሱ ሀሳቦች የሚንሸራሸሩበትና የጋራ ግንዛቤ የሚፈጠርበት መድረክ ነው፡፡
ይህ ፎረም ለመጀመሪያ ጊዜ እኤአ በ2006 በአቴንስ ግሪክ ከተደረገ በኃላ እስካሁን ድረስ 16 ግዜ በተለያዩ ሀገራት ተካሂዷል። 17ኛው ፎረም ደግሞ ከህዳር 19 እስከ 23/2015 ዓ.ም ድረስ በኢትዮጵያ ይካሄዳል፡፡
ኢትዮጵያ በምታካሂደው ጉባኤ አምስት አበይት ጭብጦች ላይ ምክክር የሚደረግ ሲሆን፤ እነዚህም፡
- ከበይነ-መረብ ግንኙነት ውጪ የሆኑ ህዝቦችን ማገናኘትና ሰብዓዊ መብትን መጠበቅና ሰዎችን ከጥቃት መከላከል፤
- ዳታን በአግባቡ ማስተዳደርና የግል ዳታ ጥበቃ፤
- የተቆራረጠ የኢንተርኔት አገልግሎትን መቅረፍ፤
- ደህንነትን ማረጋገጥ፣ ጥበቃ ማድረግና ተጠያቂነትን ማስፈን፤
- የመጪ ግዜ ቴክኖሎጂዎች የሆኑትንና እንደ ሰው ሰራሽ አስተውሎት (Artificial Intelligence) ያሉ ጉዳዮች የሚሉት ናቸው፡፡
ጉባኤውን የተመለከቱ መረጃዎችን ለመከታተል ከታች ያለውን ዌብሳይት ይመልከቱ